Saturday, October 20, 2012

ደሞ አበሻ ተነሳበት! ነቢይ መኮንን


ይኸዋ!!...ይኸዋ እንደፈራሁት
ደሞ አበሻ ተነሳበት
አየሁት ይኸው አየሁት
የኳስ ፍቅሩን ካገር ፍቅር፣ አብሮ ሲያነድ አስተዋልኩት!
አቦ እሄ ህዝብ ሆድ ያባባል፤ አቦ አበሻ ታምር ያቃል!
ጉደኛ ህዝብ ጉድ ያሳያል
ጉደኛ ህዝብ ጉድ ያፈላል!
አንዴም ውይ፣ አንደዜም እሰይ፤ ማለትን ይችልበታል!
አፈር ነክሶ፣ ትቢያ ልሶ፣ መነሳትን ያቅበታል!
በሀዘኑ ማቅ መልበስን
በደስታው ሆታ ማምጠቅን
ሁሉን በወጉ ያከብራል፡፡



ይሄዋ እንደፈራሁት፣ ይሄ ህዝብ ኅብረት ይችላል
ነይ እርግብ አሞራ!” ይላል፣ነይ አሞራ ዋንጫይላል!!

ዱሮስ ህዝብ ምን ይሳነዋል?
ገና በዋዜማው ነቅቶ፣ ተግቶ ሊጮህ ይሰማራል፡፡
ለኳሱ ላገሩ ካሉት፣ ማልዶ መሰለፍ ይችላል፡፡
ይችላል ቁሩን ይችላል፣ ቆፈን ብርዱን ይቋቋማል
እሳትን ማንደድ ይችላል፣ እሳትን መሞቅ ይችላል
ከተጨዋች እኩል ሊያምጥ
ከተጨዋች እኩል ሊሮጥ
ከአገር ልጅ እኩል ሊጋፈጥ
ከኳስ ጋር እኩል ሊለጋ
ከኳሷ እኩል ጐል ሊገባ
ልቡን ማንጠልጠል ይችላል
የድል ርሃብ ይታገሳል
አገሩ በዓለም ኳስ ሜዳ፣ መጠራቷን ይናፍቃል!
ከአጫዋች ጋር፣ ሊንጦለጦል
ከፊሽካው ጋር ሊንፎለፎል
ከአራጋቢው ሊንበለበል
ነብሱን ያንጦለጡላል
ይሄ ሁሉ ለአገሩ ሲል፣ ቆርጦ መቆሙን ያሳያል!!
ነይ እርግብ አሞራ!” ይላል፣ ነይ እርግቧ ዋንጫ ይላል!!
ህዝብማ ምን ይሳነዋል?
ንዳድ ቁጣንም ይዘልቃል
እንኳን የድል ራቡንና፣ ስንቱ ፈረንጅ የሚያማውን - የአንጀት ራቡን ይቋቋማል፡፡
ህዝብ አንድነቱን ይችላል
ጽናትን ፀንቶ ያሳያል!!
ነገም አድሮ ታግሎ ጥሎ፣ ዋንጫውን መረከብ ያቃል!
ህዝብማ ምን ያቅተዋል
ስጡኝ አይልም ይነጥቃል
በተጫዋች ማደግ መላቅ፣ በልጅ መተማመን ያቃል!!
ነይ እርግብ አሞራ!” ይላል
ይኸዋ እንደፈራሁት!
አበሽ ደሞ ተነሳበት
በስንት ዓመቷ ኢትዮጵያ፤ ደጅ አደረች ዛሬ ገና
ከስንት እግር - ኳስ ደጅ - ጥናት፣ አልፋ እንደገና ጀግና!
ደሞ ቀና ብላ ሳቀች፣ ዳግም እንደስሟ ገንና፡፡
ይኸዋ!
ይኸዋ እንደፈራሁት
ከሶስት - አሠርት በኋላ፤ ደጅ አደረች አዲሳባ
ደሞ ለድል ሆዷ ባባ
አልፋ ስንቱን ቀን ጐዶሎ፣ ስንቱን የቀን ጣይ ሸቃባ
ዳዴ ብሎ ለመታቀፍ፣ በአፍሪቃ ዋንጫው አንቀልባ!
እሳት ነደደ እስታዲዮም፣ ገና ጨዋታ ሳንጀምር
የእሳት ዳር ጨዋታ እንዲህ ነው፣ አህጉር አንጀት ውስጥ ሲጫር?
ጠብታው ጐርፍ እስከሚሆን፣ ውቂያኖስ እስኪቀላቀል
መቼም ጊዜ መፍጀቱ አይቀር፤ ባንድማ ጀንበር ድል የታል?!
ድልን ማጠራቀም እንጂ፣ አንዴ እንደአበባ አይቀጥፉም
በየጊዜው ካልገነቡት፤ ጉልበትም አይፈረጥምም
ይቀረናል ገና ድካም!
መቼም ያለመስዋዕት ድል፣ የለም ይሏልና አበውም
ጐል አባ ቁርጡን አይተናል፣ ያንን ልብ አንጠልጥል ህመም
በረኛን ያህል ገብሮ
የጐዶሎ ሙሉ ሆኖ
ታምር ነውጐል አባ ቁርጡ
ያንን ሁዳድ ሙሉ ጀግና፤ ሲገላግለው ከምጡ!”
የድልን ገድል መታደል፣ ታምር ነው ኳስ አባጃኖ
እንደ እንቁላሏ ቀስ በቀስ፤ ተወልዶ ማደግ ጀግኖ!
ጥሎ አይጥላት ይቺን አገር፣ እንደ እባብ ትቢያ እየላሰች
በእንስቷ፣ በወጣቶቿ፣ በአዋቂ ልጇ እየጠናች
ዳግም ለምልማ ፈርጥማ፣ አፍሪካን ታምሰዋለች!!
ይኸዋ እንደፈራሁት
ደሞ አበሻ ተነሳበት!
ወትሮም አመሉ ነው በቃ፣ ህዝብ አንድነቱን ያውጃል
ነገም አድሮ ታግሎ ጥሎ፣ ዋንጫውን መንጠቅ ይችላል!!
ነይ እርግብ አሞራ!” ይላል
ነይ አፍሪካ ዋንጫ!” ይላል
አበሽ ደሞ ተነሳበት!!
ነይ እርግብ አሞራ!” ይላል፡፡
ጥቅምት 4/2005
(ከአፍሪካ ዋንጫ ለተቀላቀለችው ኢትዮጵያ፣
ለኳስ ተጨዋቾቻችን እና የሀገር ፍቅር ላደለው ህዝቧ)
- በፓኤቲክ - ጃዝ ፕሮግራም ራስ ሆቴል የተነበበ
http://www.addisadmassnews.com

No comments:

Post a Comment